ኡባህ አብዱሰላም ሰኢድ
በዚህ
ጽሁፍ የአህባሽን ነገር ከሺዓ ጋር እያነጻጸርኩ እንድናየው ፈለግኩ፡፡ ከዚያ በፊት አንድ ነገር ልናገር፡፡
አንዳንድ
ሰዎች ይህንን ርዕስ ሲያዩ “ሁለቱም ጠማሞች ናቸው፤ ለምን ስለነርሱ መጻፍ አስፈለገ” ማለታቸው አይቀርም፡፡ የኔም አላማ ከሁለቱ አንዱን ለወዳጅነት እንድንመርጥ መገፋፋት አይደለም፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጻፍ የተነሳሳሁት አንዳንድ የፌስቡክ ጓደኞቼ አህባሽን ከሺዓ ጋር ሲያመሳስሉ በማየቴ አባላላቸው ስህተት መሆኑን ለማስረዳት ነው፡፡ ለዚህም የሁለቱን መመሳሰልና ልዩነታቸውን አብረን እናያለን፡፡
የአህባሽና የሺዓ መመሳሰል
አህባሽ
የሚባለው አንጃ እና የሺዓ ሙስሊሞች በሚከተሉት ነጥቦች ላይ ተመሳሳይ (ተቀራራቢ) አቋም አላቸው፡፡
1.
ሰሞኑን እንዳየነው አህባሾች ስለ “ተወሱል” እና “ተበሩክ” በሀይለኛ ሁኔታ ይከራከራሉ፡፡ ሺዓዎችም በዚህ ላይ ተቀራራቢ አቋም አላቸው፡፡ ነገር ግን ሺዓዎች ለተወሱልና ለተበሩክ የሚመርጡት “አውሊያ” ከአህሉል በይት (የፋጢማ ዛህራ እና የአሊ ኢብን አቡጣሊብ የዘር ሀረግ የተገኘ) መሆን አለበት ይላሉ፡፡
2.
አህባሾች “በአውሊያ መቃብር ላይ ደሪህ መገንባትና መቃብሮችን ዚያራ ማድረግ የአውሊያዎችን በረካ የሚያስገኙ ተግባራት ናቸው” ይላሉ፡፡ ሺዓዎችም የኢማሞችን መቃብሮች ማሳመር፤ ደሪህ መገንባት፤ ዚያራ ማድረግ ወዘተ… በጣም አስፈላጊ ተግባራት እንደሆኑ ያምናሉ፡፡
3.
አህባሾች “ከኸሊፋ አሊ ኢብን አቡጣሊብ ጋር የተዋጉ ሰሃባዎችን መሳደብና መራገም ሀጢአት የለውም” ባዮች ናቸው፡፡ ሺኣዎችም በዚህ ላይ ተመሳሳይ አቋም አላቸው፡፡
4.
በረመዳን ወር ህዝበ ሙስሊሙ ለተራዊህ ሰላት ወደ መስጊድ ሲሄድ በሀገራችን ውስጥ ያሉት አህባሾ ደግሞ “ኢልም እንማራለን” እያሉ ወደ መርከዝ ነው የሚሄዱት፡፡ “ተራዊህ ለምን አትሰግዱም?” ብሎ ለጠየቃቸው ሰው “ተራዊህ ሱንና ነው፡፡ ኢልም መማር ግን ፈርድ ነው” የሚል መልስ ይሰጣሉ፡፡ ሺዓዎች ደግሞ መስጊድ ሄደው ተራዊህን በጀመዓ አይሰግዱም፡፡ “ምክንያቱ ምንድነው?” ተብለው ሲጠየቁ “ይህ ዑመር የጀመረው ቢድአ ነው” ይላሉ፡፡
5.
አህባሾች የሚከተሉት የሱፊ ጠሪቃ “ሪፋዒያ” ይባላል፡፡ ይህ ጠሪቃ ሲልሲላውን (የሼይኾች የቅብብሎሽ መንገድ) ከነቢዩ ጋር የሚያገናኘው የሺዓ አማኞች አስራ ሁለቱ ኢማሞቻችን ናቸው የሚሏቸውን ሰዎች በመቁጠር ነው፡፡
6.
አህባሾች ለመውሊድ ከልክ ያለፈ ፍቅር አላቸው፡፡ ለህጋዊነቱም ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከራሉ፡፡ የነቢዩንና (ሰ.ዐ.ወ) የፋጢማ ዛህራን (ረ.ዐ) መውሊድ ጨምሮ ሌሎች በርካታ መውሊዶችን ያከብራሉ፡፡ ሺዓዎችም መውሊድን በጣም ይወዳሉ፡፡ እንዲያውም መውሊድ ራሱ የተጀመረው በአህሉ ሱንና ሰዎች ሳይሆን ግብጽን ከ10ኛው-11ኛው ክፍለ ዘመን ድረስ ባስተዳደሩት የፋጢሚይ ገዥዎች ነው፡፡ ፋጢሚዮች ደግሞ ሺዓዎች እንጂ ሱኒዮች አልነበሩም፡፡
7.
አህባሾች ሼይኹል ኢስላም ኢብን ተይሚያህንና ሼይኽ ሙሀመድ ኢብን አብዱልወሃብን በጣም ይጠላሉ፡፡ ሺዓዎችም በነዚህ ምሁራን ላይ ተመሳሳይ አቋም ነው ያላቸው፡፡
የአህባሽና
የሺዓ መመሳሰል ከብዙ በጥቂቱ ይህንን ይመስላል፡፡ ይሁንና አህባሾች እነኝህን አቋሞች የወረሱት ከሺዓዎቹ አይመስለኝም፡፡ ከዚህ በፊት እንደገለጽኩት “አህባሽ” የሚባለው ፓርቲ ራሱ የተቋቋመው የአንጃው መስራች የሆኑት ሼኽ አብዱላህ አል-ሀረሪ በተበሩክ፤ ተወሱል፤ የመቃብር ዚያራ ወዘተ.. ላይ ለነበራቸው የተዛነፈ አቋም ሸሪአዊ መልክ ለማስገኘት በመፈለጋቸው ነው፡፡
ሰሀባዎችን
መስደብና ተራዊህን ዝቅ አድርጎ ማየት ደግሞ ከሺዓዎች የተወረሰ ሳይሆን “አለዊ” የሚባሉትን የሶሪያ ገዥዎች ለማስደሰት የተወሰዱ አቋሞች ይመስሉኛል፡፡ (ኡለማ ሙሉ በሙሉ ካፊር ነው በማለት የፈረጁት ይህንን አለዊ የሚባለውን “ፊርቃ” ነው፡፡ ሺዓዎችም ሆኑ ሱኒዮች “አለዊ ካፊር እንጂ ሙስሊም ቡድን አይደለም” በሚለው ላይ ተስማምተዋል፡፡)
የአህባሽና የሺዓ ልዩነት
አህባሾችና ሺዓዎች በሚከተሉት ነጥቦች ላይ ከፍተኛ ልዩነት አላቸው፡፡
1.
አህባሾች የሚጠሉት እነ ኢብን ተይሚያህን ብቻ አይደለም፡፡ እነርሱ የሚወዷቸውን የአውሊያ መቃብሮች ያልነኩባቸውን እንደ ጀማሉዲን አል-አፍጋኒ፤ ረሺድ ሪዳ፤ አቡል አእላ መውዱዲ፤ ሰይድ ቁጥብ፤ ወዘተ የመሳሰሉ ምሁራንና ሙስሊም ታጋዮችንም በጣም ይጠላሉ፡፡ ሺዓዎች ግን ለነኝህ የተሀድሶ አራማጆችና የሙስሊም ህብረት አስተማሪዎች ከፍተኛ አድናቆት አላቸው፡፡ ለምሳሌ የቀድሞው የኢራን መሪ አያቱላህ ሩሑላህ ኾሜይኒ የአቡል አእላ መውዱዲን መጽሀፍት ከመውደዳቸው የተነሳ አንዳንዶቹን ወደ ፋርሲ (ኢራን) ቋንቋ ተርጉመዋል፡፡
2.
አህባሾች በዚህ ዘመን የሸሪአ ህግን የሚተገብር መንግስት መመስረት አይቻልም ባይ ናቸው፡፡ “የኸሊፋዎች አይነት አስተዳደርም ሆነ ኢስላማዊ ሪፐብሊክ መመስረት አይቻልም፡፡ ስለዚህ ሀይማኖቱን ብቻ ይዘን ከፖለቲካው መገለል አለብን” ባይ ናቸው፡፡ በአህባሽ አመለካከት መሰረት ጂሀድ እናካሂዳለን የሚሉት የሙስሊም ነጻነት ንቅናቄዎችም ጊዜ አልፎባቸዋል፡፡
ሺዓዎች ግን ከዚህ ተቃራኒ የሆነ አመለካከት ነው ያላቸው፡፡ “የሸሪዓ ህግ ከየትኛዉም ዘመን ጋር የሚሄድ ወደር የለሽ ህግ ነው፤ በርሱ የሚመራ ኢስላማዊ መንግስት መመስረትም ይቻላል” ባይ ናቸው፡፡ “ጂሀድም ቢሆን ጥቃት ባለበት ጊዜ ሁሉ መካሄድ አለበት” ይላሉ፡፡
3.
አህባሾች በጣም ጽንፈኛ ናቸው፡፡ ከነርሱ ጋር የማይራመድ፤ የነርሱን ሀሳብ የማይቀበል፤ እነርሱ ሸሪአዊ መልክ ሰጥተው የሚያደርጉትን ድርጊት የሚቃወም ሁሉ “ካፊር” ነው፡፡
ሺዓ ግን እንዲህ አይልም፡፡ ማንም ሰው “ላ ኢላሀ ኢለላህ ሙሐመዱን ረሱሉላህ” ብሎ ካመነ ሙስሊም ነው፡፡ ከነርሱ የሚለዩትን ሙስሊሞች “መንገዱን ለቀዋል፤ ተሳስተዋል” ነው የሚሉት እንጂ “ካፊር” ያሉበት ወቅት የለም፡፡
4.
አህባሾች ከሙስሊሞች ይልቅ ሙስሊም ያልሆኑ ወገኖችን ይጎዳኛሉ፡፡ የነርሱ ጓደኞች ምዕራባዊያን፤ ጽዮናዊያን፤ የሶሪያው አለዊ (ኑስራኒ) ሀይማኖት ተከታዮች ወዘተ.. ናቸው፡፡ ሺዓዎች ግን እንዲህ አይነት አመል የለባቸውም፡፡ ሚስጢራቸውን እርስ በራሳቸው እንጂ ከአላህ ጠላቶች ጋር አያወሩም፡፡
5.
አህባሾች ዋነኛ ጠላታችን “ወሃቢያ” ነው ይላሉ፡፡ በነርሱ አመለካከት “እስልምናን እያጠፋ ያለውና ወደፊትም የሚያጠፋው “ወሀቢያ ነው”፡፡ በመሆኑም ወሃቢ የሚሉትን ሰው ለአላህ ጠላቶች አሳልፎ ከመስጠት ወደኋላ አይሉም፡፡
ሺዓዎች ግን “ዋነኛው የኢስላም ጠላት ጽዮናዊያንና ተባባሪዎቻቸው ናቸው” ይላሉ፡፡
ከላይ ከቀረበው ንፅፅር እንደምንረዳው መጥፎ የሚባለው ነገር ሁሉ መጥፎነቱ እኩል አይደለም፡፡ ከመጥፎው ሁሉ የተሻለ መጥፎ አለ፡፡ ከመጥፎዎች ሁሉ የሚበልጥ የመጥፎ መጥፎ አለ፡፡
“አህሉሱንና ወል-ጀመዓ” ነኝ የሚለው አህባሽ ከኛ ጋር በብዙ መልኩ የሚለያየውን የሺዓ አንጃ ያህል እንኳ ለኢስላም አይቆረቆርም፡፡ ሺዓዎች የኢስላም ጠላቶች “ጽዮናዊያን ናቸው” ነው የሚሉት፡፡ አህባሽ “የኢስላም ጠላቶች ወሀቢዎች ናቸው ይላል”፡፡ አስተግፊሩላህ!!
የአህባሽ ጠላቶች እኛ ሙስሊሞች ነን፡፡ አላህ ብቻ አይጣላን እንጂ አህባሽና ግብረ አበሮቹ እንደፈቀዳቸው ይበሉን፡፡ እኛ በአላህ ስለምናምን እንደ አህባሽ የኢስላምን ክብር ለአላህ ጠላቶች አናስረክብም፡፡
ድል የኢስላም ነው፡፡ አላሁ አክበር!!!!
No comments:
Post a Comment