Ubah Abdusalam Seid
እነዚህ አህባሾች ቀላል ህዝቦች እንዳመስሏችሁ!! አባላቶቻቸው ሀቁን እንዳይመለከቱ በበርካታ መጋረጃዎች ይጋርዷቸዋል፡፡ እነርሱ የሚጠሉትን ሰውና ግለሰብ ሌላው ሰው እንዳይቀበለው ለማስጠነቀቅ በርካታ “ተረቶችን” ያስወሩባቸዋል፡፡ ለዛሬው አህባሾች “ወሀቢያ” በሚሉት ቡድን ላይ ከሚያስወሯቸው ተረቶች አንዱን እናያለን፡፡
የ”ቱርኮች” ያልተረሳ ቂም
ወደ ዋናው ጉዳይ
ከመግባታችን በፊት እስቲ ስለ ታሪክ ትንሽ እናውራ፡፡
አብዛኛውን የአረቢያ ልሳነ-ምድር የምትሸፍነው የዛሬዋ ሳኡዲ አረቢያ ከ18ኛው እስከ 20ኛው ክፍለ ዘመን መገባደጃ ድረስ የሀይለኛ ጦርነቶች አውድማ ነበረች፡፡ በጦርነቱ በዋናነት የሚዋጉት ሂጃዝ የተባለውን ክፍለ-ሀገር የሚያስተዳድሩት ከነቢዩ የዘር ሐረግ እንደተወለዱ የሚናገሩት የ“ሸሪፍ አሊ” ቤተሰቦችና ነጅድ የተሰኘውን በረሀማ ክልል የሚገዙት የአል-ሱዑድ ቤተሰቦች ነበሩ፡፡ ታዲያ በሚገርም ሁኔታ የነጅድ ገዥዎች ከማንም ተጽእኖ ነጻ ነበሩ፡፡ የሂጃዝ ገዥዎች ግን ተጠሪነታቸው የዘመኑ ሀያል ገዥ ለነበረው የቱርክ ሱልጣን ነው፡፡ የነጅድ ገዥዎች እያሸነፉ መካና መዲናን በያዙ ቁጥር ግዙፉ የቱርክ ጦር እየበረረ ይመጣና ያስወጣቸዋል፡፡ ከዚያም ሀገሩን ለሸሪፎች ያስረክባል፡፡
ጦርነቱ እንዲህ እያለ እስከ ሀያኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ድረስ ዘለቀ፡፡ በመጨረሻም ቱርክ በአንደኛው የአለም ጦርነት ስትገባ የሀይል ክፍተት ተፈጠረ፡፡ ከነጅድ የተነሳው የሳኡዲ ጦር ይህን አጋጣሚ በመጠቀም የሂጃዙን የሸሪፍ ቤተሰብ ድል በማድረግ ከሀገሩ አባረረ፡፡ በኋላም ከኸሊፋዎች ዘመን ወዲህ በአንድ መንግስት ስር ተሰባስቦ የማያውቀውን የአረቢያ በረሃ አንድ ላይ በማጠቃለል “አል-መምልከቱል ዐረቢያቱስ ሳዑዲያ” (Kingdome of Saudi Arabia)
የተባለ
ሀገር
መሰረተ፡፡ ከሂጃዝ የተባረረው የሸሪፍ አሊ ቤተሰብ ደግሞ ወደ ዮርዳኖስ በማቅናት ዛሬ “መምለከቱል ሀሺሚያቱል ኡርዱኒያ” (Hashimite Kingdom of Jordan) የሚባለውን ሀገር ፈጠረ፡፡
ሳኡዲዎች በዚያ ዘመን የተደረገውን ጦርነት የጀግንነታቸው መገለጫ አድርገው ይቆጥሩታል፡፡ “ሳኡዲ አረቢያ ዛሬ ለደረሰችበት እድገት መሰረት የሆናት ንጉስ ሙሀመድ ኢብን ሱኡድ በሸሪፎቹ እና በቱርኮቹ ላይ ያሳየው አልገዛም ባይነት ነው” ይላሉ- ሳኡዲዎች፡፡ የዮርዳኖስ ንጉሳዊያን ቤተሰቦችና ቱርኮች ግን የያኔውን ጦርነት እንደ ክፉ ጠባሳ ይቆጥሩታል፡፡ እንዲያውም “ጦርነቱን የፈጠሩትና በጦርነቱ የተሳተፉት ሁሉ የነቢዩን ቤተሰቦች የሚጠሉና እስልምናን ለማጥፋት የተነሱ የይሁዲ ወኪሎች ናቸው” ይላሉ፡፡ ይህንን ነገር በሰፊው የሚተርኩት ግን ቱርኮች ናቸው፡፡
“ቱርኮቹ ለምን እንዲህ ያመርራሉ?” ካልን በቂ መልስ የለንም፡፡ እነርሱ ምክንያቱን ሲያስረዱ ግን “ያንን የመሰለ ግዛታችንን የበጠበጠውና በመላው ሙስሊም ዓለም የነበረንን ተቀባይነት ያረከሰው ከነጅድ የተነሳው የወሃቢ ሀይል ነው” ይላሉ፡፡ ለመሆኑ ወሃቢ ያኔም ነበረ?
የሰላዩ ማስታወሻ
ከዚህ በፊት በጻፍኩት አንድ ጽሁፍ አህባሾች “ወሀቢያ የተፈጠረው በሙሐመድ ኢብን ሱኡድ እና በሙሀመድ አብዱል ወሃብ አማካኝነት ነው፤ ሁለቱን ሰዎች መልምሎ በማሰልጠን ለግዳጅ ያሰማራው አንድ እውቅ እንግሊዛዊ ሰላይ ነው” ይላሉ” በማለት ገልጬ ነበር፡፡ በእውነትም ይህ ታሪክ ለአንድ የአህባሽ ምልምል አባል የሚነገረው ገና ወደ ቡድኑ እንደተጠጋ ነው፡፡ ስለ“ወሃቢያ” መጥፎነት ለማስረዳት የመጀመሪያ ማስረጃ ሆኖ የሚቀርበውም ይህ ታሪክ ነው፡፡
ይህንን ታሪክ የሚተርክ መዝገብም ሆነ መጽሀፍ ለረጅም ጊዜ ሳፈላለግ ሊቀናኝ አልቻለም ነበር፡፡ አሁን ተሳክቶልኝ አግኝቼዋለሁ፡፡ እናንተም ሙሉ መጽሀፉን ከሚከተለው ድረ ገጽ ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
የመጽሀፉ ርዕስ “Memoirs of Mr. Hempher, The British Spy To The Middle East” ይሰኛል፡ ይህ መጽሀፍ ሚስተር ሄምፈር በሚባል እንግሊዛዊ ሰላይ ነው የተጻፈው ይባላል፡፡ ሰውየው መጽሀፉን የጻፈው ድሮ በሰራው ስራ ጸጸት ስለገባው ነውም ተብሏል፡፡ ሚስተር ሄምፈር (የአባቱ ስም አልተገለጸም) እንደሚለው “የእንግሊዝ መንግስት ሙስሊሞች ጠንካሮች ናቸው፡፡ እነርሱን ለማጥፋት ከውስጣቸው ገብተን መበታተን አለብን፡፡” ከሚል አቋም በመነሳት ወደ መካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ለስለላ ላከኝ፤ በአንድ ጉዞዬ መሀመድ አብዱል ወሀብ ከሚባል ወጣት ተማሪ ጋር በበስራ ከተማ ተዋወቅኩ፡፡ ከዚያም በእስልምና ውስጥ አክራሪ የሆነ አዲስ አንጃ እንዴት መፍጠር እንደሚቻል ሰፊ ስልጠና እየሰጠሁ ለግዳጅ አሰማራሁት” ይላል፡፡
እንግዲህ ሙሀመድ አብዱል ወሃብና ሙሀመድ ኢብን ሱኡድ ሙስሊሙን ከውስጥ ሆነው እንዲያጠቁ የተላኩ የእንግሊዝ ምንደኞች ናቸው ማለት ነው፡፡ ዛሬ ከሳኡዲ አረቢያ ወደ ልዩ ልዩ ሀገራት ኤክስፖርት የሚደረገው የ“ወሀቢያ” ትምህርትም በእንግሊዝ የተፈበረከ መርዝ መሆኑ ነው፡፡ ለመሆኑ የተባለው ነገር እውነት ነው?
የመጽሀፉ እርግጠኝነት
አህባሾች ስለዚያ መጽሀፍ ከነገሩኝ በኋላ በነገሩ ላይ ስንወያይ “ይህ የምታወሩት ወሀቢያ የሚባለው ነገር ስለመኖሩ ራሱ እጠራጠራለሁ” አልኳቸው፡፡ እነርሱም ወዲያኑ በ“ወሀቢያ” ታሪክ ዙሪያ የተጻፈ ሌላ መጽሀፍ ሰጡኝ፡፡
የዚያኛው መጽሀፍ ርእስ “Wahhabism: A Critical Essay” ይሰኛል፡፡ የመጽሀፉ ደራሲ ፕሮፌሰር ሀሚድ አልጋር የሚባሉ ታዋቂ የ“ሺዓ” ምሁር ናቸው፡፡ ታዲያ ደራሲው በመጽሀፋቸው የ”ወሀቢያ ሀቅ” ነው ያሉትን ታሪክ በሰፊው ይተርኩና በአንደኛው ገጽ የግርጌ ማስታወሻ ከላይ የጠቀስኩትን የሚስተር ሀምፈር ታሪክ ያነሱታል፡፡ በመደምደሚያቸውም “ያ መጽሀፍ ፎርጅድ ሳይሆን አይቀርም” ይላሉ፡፡
አህባሾች የሚያወሩት ነገር ከግማሽ በላይ ሀሰት ነው፡፡ ስለ ሚስተር ሀምፈር የተነገረኝን ነገር የሰማሁትም እየጎረበጠኝ ነው፡፡ በኋላ የሺዓው ምሁር (“የወሀቢ ጠላት ነኝ” ነው የሚሉት) በጨረፍታ የተናገሩት ነገር ትልቅ ማስጠንቀቂያ ሆነኝ፡፡ እስከቅርብ ጊዜ ድረስ መጽሀፉን ባላነበውም ወሬው በሀሰት የተፈጠረ መሆኑ ገብቶኛል፡፡ ለመሆኑ ወሬውን ማን ፈጠረው?
ዊኪፒዲያ እንደሚለው ይህንን የፈጠራ መጽሀፍ ጽፎ ያሰራጨው አዩብ ሰብሪ ፓሻ የሚባል የኦቶማን ቱርክ የባህር ሀይል ባልደረባ ነው፡፡ በንጉስ ሙሐመድ ኢብን ሱኡድ እና በሼይኽ ሙሀመድ አብዱል ወሃብ የተቀጣጠለው የለውጥ አብዮት ቱርኮችን በአረቢያ ከነበራቸው ግዛት ላይ ሲያባርራቸው በምቀኝነት ይህንን የፈጠራ ወሬ አሰራጩ፡፡
በሌላ በኩል በርካታ ሙስሊም ምሁራን ይህ ተጻፈ የሚባለው መጽሀፍ “እውነት መሆኑን እናጣራ” በማለት በታላላቅ የአውሮፓ ቤተ መጽሀፍት አሰሳ አድርገው ነበር፡፡ በተለይ ቀደምትና ጥንታዊ መጽሀፍት የሚቀመጡባቸውን ክፍሎች ፈትሸዋል፡፡ ሆኖም ሚስተር ሀምፈር በሚባል ስም የተመዘገበ ተመሳሳይ ርእስ ያለው መጽሀፍ አላገኙም፡፡ ስለዚህ “የፈጠራ ተረት ነው” ከሚል መደምደሚያ ላይ ደርሰዋል፡፡
ህጸጹ (fallacies)
መጽሀፉ በፈጠራ የተጻፈ መሆኑን በውስጡ ካሉት በርካታ ህጸፆች (fallacies) መረዳት ይቻላል፡፡
ለምሳሌ
·
መጽሀፉ ሙሀመድ ኢብን አብዱል ወሃብ “ይሁዲ ናቸው” ይላል፡፡ ነገር ግን ሼኽ ሙሐመድ አብዱል ወሃብ “ተሚም ከተባለ ጎሳ የተወለዱ አረብ ናቸው፡፡
·
መጽሀፉ ሼይኽ ሙሀመድ ኢብን አብዱል ወሃብ “አረብኛ፤ ፋርሲ እና የቱርክ ቋንቋ ይናገራሉ” ይላል፡፡ ሆኖም ሼይኽ ሙሀመድ ኢብን አብዱል ወሃብ ከአረብኛ ውጪ ሌላ ቋንቋ በፍጹም አይናገሩም፡፡
·
መጽሀፉ እንደሚለው ሚስተር ሀምፈር ከወጣቱ ሙሀመድ አብዱል ወሃብ ጋር በበስራ ከተማ የተገናኘው በ1712 ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ ዓመት ሙሀመድ ኢብን አብዱል ወሃብ እዚያው በተወለደበት አካባቢ የሚኖር የዘጠኝ ዓመት ህጻን ነበር፡፡ ሰለዚህ ከቤተሰቦቹ ተነጥሎ ወደ በስራ ሄደ የሚለው ተረት አይሰራም፡፡
·
ሌላው ቀርቶ በመጽሀፉ ላይ የተጠቀሰው “በእንግሊዝ ግዛት ላይ ጸሀይ አትጠልቅም” የሚለው አባባል እጅግ በጣም ዘግይቶ በ20ኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ የመጣ ነው እንጂ በዚያ ዘመን እንዲህ አይነት አባባል አልነበረም፡፡ በወቅቱ እንግሊዝ በእስያና በአፍሪካ ምድር አንድም ኮሊኒ (ቅኝ ግዛት) አልነበራትም፡፡
አህባሾች እንግዲህ ይህንን በተረት የታጨቀውን ተራ ወሬ ነው እንደ ግዙፍ ነገር አድርገው የሚያስተጋቡት፡፡ በነርሱ ቤት የማይነቃባቸውና እውነታው የማይገለጽ መስሏቸዋል፡፡ ፈጠራ፤ ተረት፤ ሀሰት ወዘተ… የሙናፊቆችን ቀልብ ሊማርክ ይችላል፡፡ የሙእሚኖችን ልብ በፈጠራና በተረት መክፈት አይቻልም፡፡
በመጨረሻ! ይህ አይነ-ደረቅ የሆነ የኑፋቄ ቡድን አባላቶቹን ይዞ መቀጠል እጅግ ይከብደዋል፡፡ ምክንያቱም እርሱ ውሸትን እንደሚፈልገው እየቀጣጠፈ ሲሄድ አባላቱ እየነቁበት “ወራጅ አለ!” ይሉታል፡፡ ከዛሬ በኋላም በርሱ ዙሪያ የተሰበሰቡ ወንድሞችና እህቶቻችን “ውሸቱን” እየነቁ “ወራጅ አለ” እንዲሉት እንጠይቃቸዋለን፡፡
No comments:
Post a Comment